2014 ጁን 24, ማክሰኞ

ባለፈው የፊልጵስዩስ ጥናት የወንጌል መስፋት የደስታው ምክንያት
መሆኑን አይተን ነበር። ይህ ክፍል ከዚያ የደስታ መፍሰስ የቀጠለ ነው።
ቀጣይ ደስታው ከወንጌል ስብከትና ስፋት ያለፈም ነው። አሁን የራሱን
መዳን ፍጹምነት እያሰበም፥ ለነዚህ ሰዎች ያለውን አገልግሎት እያሰበም
ይደሰታል። ክርስትና ደስታ ነው። ወደ ኋላ አይተን ስለመዳናችን፥
ባለንበት ሁኔታም ከጌታ ጋር በመገኘታችን፥ ወደፊትም ወደ አባቱ ደስታ
የምንገባ በመሆናችን እንደሰታለን።
ቁጥር 19፤ ወደ ፊትም ደግሞ ደስ ይለኛል፤ ይህ በጸሎታችሁና በኢየሱስ
ክርስቶስ መንፈስ መሰጠት ለመዳኔ እንዲሆንልኝ አውቃለሁና፥ ይህ
ናፍቆቴ ተስፋዬም ነውና፤ በአንድ ነገር እንኳ አላፍርም ነገር ግን
በሕይወት ብኖር ወይም ብሞት፥ ክርስቶስ በግልጥነት ሁሉ እንደ
ወትሮው አሁን ደግሞ በሥጋዬ ይከብራል።
ለመዳኔ ሲል አልዳነም ነበር ወይም ደኅንነቱ ገና የተረጋገጠ አልነበረም
ማለት አይደለም። ከእስር ቤት ስለመፈታቱም መናገሩ አይደለም።
ከእስር ስለመፈታት አለመሆኑን ቃሉን ቀጥለን ስናነብብም እንረዳለን።
ስለሞቱ እየተናገረ ስለመፈታት ሊናገር አይችልም። እርግጥ እንደሚፈታ
ተስፋ ያደርጋል፤ (ቁ. 25 እና 2፥24)። እንኳን ያለ ወንጀል የታሰረ የጌታ
እስረኛ ወንጀል የፈጸመውም ለመፈታት ተስፋ ቢያደርግ ማስገረም
የለበትም። ቃሉ ግን σωτηρίαν (ሶቴሪያን) ከክፉ መጠበቅንና ነጻ
መሆንንም ጭምር ቢያመለክትም ዋና አሳቡ ድነት ወይም መዳን ነው።
ቃሉ በክርስቶስ ያገኘነው መዳን የተገለጠበት ዋናው ቃል ነው። ክርስቶስ
መድኃኒት ወይም አዳኝ ሲሰኝም ይኸው ቃል (ሶቴር) ነው የተጻፈው፤
ጳውሎስም ራሱ ይህን ቃል በ3፥20 ጽፎታል። ስለዚህ ሐዋርያው ከእስር
ስለመውጣቱ መዳን መናገሩ አይደለም።
በዚሁ ምዕራፍ ቁጥር 6ን ስናጠና ጌታ ጀማሪም ፈጻሚም አምላክ
መሆኑን አስተውለን ነበር። ይህ የተጀመረ ሥራም የደህንነታችን ጉዳይ
መሆኑን አይተናል። በፊል. 2፥12ም ይህንን መዳንን የመፈጸም ቃል
ይናገራል። ይህ መዳን መጠበቅ፥ መፈጸም፥ መጨረስ፥ ፍጹም መደረግ
ያለበት ነገር ነው። ይህ የጳውሎስ መዳን እንግዲህ የመዳን መቀጠል
ወይም በደኅንነት ውስጥ ሆኖ የመኖር ሁኔታ ነው። በቅድስና የማደግንን፥
በመከራ የመጽናትን፥ የሰማዩን የመናፈቅን፥ ባሉበት ቦታና ሁኔታ ለእርሱ
ክብር መኖርን፥ በዚህም ሁሉ ያ ሰው የዳነ ሰው መሆኑን አመልካች
ነው። ጳውሎስ መታሰሩና በመታሰሩም ምክንያት በገዛ ሕይወቱም ሆነ
በወንጌል መስፋት ምክንያት በሌሎች ሰዎች ሕይወት ውስጥ የሆኑት
ነገሮች የመዳኑ መገለጫዎች ናቸው።
እነዚህ ነገሮች እንዴት ወይም በምን ኃይል እንደሚሆኑ ሲናገር፥
በጸሎታችሁና በኢየሱስ ክርስቶስ መንፈስ መሰጠት አለ። መዳናችንን
በፍሬያማነት ቀጣይ ለማድረግ እነዚህ ሁለት እጅግ አስፈላጊ ነገሮች
ናቸው። የቅዱሳን ጸሎት በመንፈሳዊ ጉዞአችንና በአገልግሎታችን
ብርታትና ልቀት ውስጥ ሁነኛ ሚና አለው። የኛም ጸሎት በሌሎቹ
ሕይወት ውስጥ የሚሠራው ድንቅ ሥራ አለው። ሌሎች እንዲጸልዩልን
መጠየቅን፥ እኛም ለሌሎች ቅዱሳን መጸለይን አናቋርጥ።
ሌላው ቃል ἐπιχορηγίας (ኤፒኮሬጊያስ) የሚል ነው። መደገፍንም
መስጠትንም የሚገልጥ ἐπιχορηγέω ከሚል ቃል የመነጨ ነው።
መስጠትን ሲገልጥ፥ መስፈር፥ ማቅረብ፥ መሙላት ማለት ነው።
መደገፍም ማቆም፥ ማበርታት፥ እንዳይንገዳገዱ እንዳይወድቁ መያዝ
ነው። ይህን የሚያደርግ ደግሞ የኢየሱስ መንፈስ ነውና ይህን መንፈስ
ታመነ። የኢየሱስ መንፈስ ከመንፈስ ቅዱስ ስሞች አንዱ ነው።
የፊልጵስዩስን መልእክት መግቢያ ከሐዋ. 16 ስንመለከት በተለይ ቁጥር
6-7 ላይ ይህንን አይተን ነበር። የኢየሱስ መንፈስ የሚለው ቃል በዚያ
እና እዚህም ይገኛል። የሚናገረው ስለ መንፈስ ቅዱስ ሆኖ ሰጪው
ኢየሱስ መሆኑን መግለጡ ነው። እግዚአብሔር መንፈሱን ሰፍሮ፥ ለክቶ፥
ቆጥቦ አይሰጥም (ዮሐ. 3፥34)። ክርስቲያን በመንፈስ ቅዱስ ቁጥጥር
ወይም ሙላት ስር ሆኖ መኖር ሁሌም የሚጠበቅበት ኑሮ ነው።
በክርስቲያን ሕይወት ውስጥ የመንፈስ ቅዱስ ሙላት የአንድ ቀን ክስተት
ሳይሆን የየእለቱ የራስ ድካም በእርሱ ብርታትና ሁሉን ቻይነት፥ የራስ
አለማወቅ በእርሱ ሁሉን አዋቂነት የሚፈጸምበት ሕይወት ነው።
የመንፈስ ቅዱስ መሰጠትና ሙላት ሕይወት ነው፤ ኑሮ ነው፤ የክርስቶስ
በኛ ውስጥ መኖር፤ የኛም ለክርስቶስ መኖር ነው። የመዳናችን መዳን
እንደሆነ የማለቁ፥ የመፈጸሙ አካሄድ ነው።
ጳውሎስ እነዚህን ሁለት ትልልቅ ነገሮች፥ የቅዱሳንን ምልጃ እና
የክርስቶስን መንፈስ መሰጠት መናፈቁ በመከራውና በእስራቱም ውስጥ
ለክርስቶስ ለመኖርና እስከ ፍጻሜውም ለመጽናት የቆረጠ የቁርጥ ሰው
መሆኑን አመልካች ነው። ይህ ናፍቆቱም ተስፋውም ነው። ይህ ናፍቆቴ
ተስፋዬም ነውና አለ። ናፍቆትና ተስፋ የተለያዩ ግን ተቀራራቢ ነገሮች
ናቸው። ናፍቆት ምኞት ነው፤ ሊፈጸምም ላይፈጸምም ይችላል። ግን
ቃልህ ተገኝቶአል እኔም በልቼዋለሁ አቤቱ፥ የሠራዊት አምላክ ሆይ፥ በስምህ ተጠርቻለሁና ቃልህ ሐሤትና የልብ ደስታ ሆነኝ። ኤር. 􀅦 􀆉፥􀅦 􀆊 6
ቁጥር 􀅦 􀆇 - ኅዳር ፪ሺህ ፬ ዓመተ ezralit@gmail.com ምሕረት NOVEMBER 2011
የውስጣችን መሻት ነው። ተስፋ ግን የሚፈጸምና በተስፋ ሰጪው ላይ
የሚደገፍ ቃል ነው። ተስፋ ሰጪው የታመነ ከሆነ ተስፋው ይፈጸማል፤
ካልሆነ ደግሞ ይቀራል። ጳውሎስ በታሰረበት ወኅኒ ውስጥ ይሁን ወይም
ተፈትቶ፥ በሕይወት ይኑር ወይም ሞቶ ግቡ አንድ ነው፤ እርሱም
የክርስቶስ ክብር። በአንድ ነገር እንኳ አላፍርም ነገር ግን በሕይወት
ብኖር ወይም ብሞት፥ ክርስቶስ በግልጥነት ሁሉ እንደ ወትሮው አሁን
ደግሞ በሥጋዬ ይከብራል አለ።
ስለዚህ ለጳውሎስ መኖርም መሞትም ክርስቶስ እስከከበረ ድረስ ትልቅ
ልዩነት የላቸውም። እንዴት ድንቅ ነው! ክርስቲያኖች የምንኖርለት ብቻ
ሳይሆን የምንሞትለትም ምክንያት ያለን ሰዎች ልንሆን ነው የተጠራነው።
ለምንኖርለት ዓላማ ለመሞትም ካልቆረጥን ልንኖርለት አንችልም። ይህ
እውነት ነው። ለምን ቢባል ቁርጠኞች ካልሆንን እምነታችን የተግባር
ሳይሆን የአፍ ብቻ ነው ማለት ነው። ለምንኖርለት ነገር ልንሞት
ከተጠየቅን አንሞትማ! እንሸሻለና! ስለዚህ መኖራችን የለበጣ ነው።
ስለ ሚሊሻ በድሉ ልንገራችሁ። ያኔ የኢትዮ-ሱማሌ ጦርነት ጊዜ አንድ
በድሉ የተባለ ሚሊሻ ወታደር ነበረ አሉ። አንድ ቀን የብርጌዱ አዛዥ
የሆኑት ኮሎኔል፥ “እነዚህን ሽርጣም ሱማሌዎች ማየት እንዳስጠላኝ ያለ
ሌላ የሚያስጠላኝ ነገር የለም። ዛሬ ያንን ኮረብታ ሄደን መያዝና እዚያ
የመሸጉትን ሽርጣሞች ጨርሰን መደምሰስ አለብን፤ እሺ ጎበዝ?” አሉ።
ሁሉም፥ አብዮታዊት እናት አገር ወይም ሞት! ሞት! ሁሉም ነገር
ለአብዮቱ! . . . አሉና አንዳንዶቹም ፎከሩና ዘመቻው ተጀመረ። ሚሊሻ
በድሉ አፈግፍጎ ወደ ሰፈር ሲሸሽ ተያዘና ማታ ኮሎኔሉ ዘንድ ቀረበ። ይህ
የወታደሩን ወኔ የሚሰልብ ድርጊት በመሆኑ አዛዡ በቁጣ፥ “እህ ሚሊሻ
በድሉ፥ ለምን ሸሸህ?” አሉት። ሚሊሻ በድሉም፥ “ጌታዬ ኮረኔል፥ እኔም
እንደርስዎ እነዚህን ሽርጣም ሱማሌዎች ማየት እንዳስጠላኝ ያለ ሌላ
የሚያስጠላኝ ነገር የለም፤ ገና ከሩቅ ሳያቸው አስጠሉኝና ጥያቸው ወደ
ሰፈር መጣሁ” አለ።
ሚሊሻ በድሉ ይቅርታ ተደረገለትና ከሠራዊቱ ጋር ቆየ። በሌላ ቀን
ኮሎኔሉ አቅርቦ በሚያሳይ በመነጽራቸው አንድ ጉብታ ላይ አራት ቃኚ
ሱማሌዎች ያያሉ። ከወታደሮቻቸው አራቱን ይመርጣሉ። ሦስቱ ደፋሮች
ናቸው፤ አንዱ ጉብዝናው መፈተሽ ያለበት ሚሊሻ በድሉ ሆነ። ኮሎኔሉ
አራቱን ወደፊት ጠርተው፥ “እዚያ ጉብታ ላይ አራት ሱማሌዎች አሉ፤
እናንተ አራታችሁ ዛሬ አብዮታዊ ወኔያችሁን የምታስመሰክሩበት ቀን
ነው፤ እናንተም አራት፤ እነሱም አራት፤ በሉ ግደሉና መሳሪያቸውን
ይዛችሁ ኑ!” ብለው ሲያሰናብቷቸው አንዱ ወታደር፥ “ኮሮሌር፥ ኢኔ
ሁላት ጋዲሎ ሁላት ማሳራ ዪዞ ዪማላሳል!” አለ። ይኸኔ ሚሊሻ በድሉ፥
“ጎሽ የኔ ጅግና! እንዲያው እናት አንተን ደጋግማ መንታ አድርጋ
ትውለድ! በቃ!” ብሎ አጨበጨበለትና ወደ ኮሎኔሉ ዞሮ፥ “ኮረኔል የኔን
ፋንታ ደበላ ስለሚገልልኝ እኔ ቀርቻለሁ፤ ሁለተኛውን ሽርጣም
የሚገድልበት ሌላ መሳሪያ ከፈለገም ይኸው የኔን ክላሽ እሰጠዋለሁ”
አለ። ሚሊሻ በድሉ በሞት ቀበሌ የሚኖር ሞትን አጥብቆ የሚፈራ ሰው
ነው። ጳውሎስ ከሞት ጋር ሳይፈራ የተጋፈጠ ሰው ነው።
21፤ ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና።
ለጳውሎስ የኑሮና የአገልግሎቱ፥ የጥሪና የተልእኮው መለኪያ የክርስቶስ
ክብር ነው። ስለዚህ ሞትም ሕይወትም ልዩነት የላቸውም። ለእርሱ
ሕይወት ክርስቶስ ነው፤ የሚኖረው ለክርስቶስ ነው፤ የሚሞተውም
በክርስቶስ ውስጥ ሆኖ ነው። የጳውሎስ ሕይወት የሚያጠነጥንበት አንድ
እንዝርት፥ የሚሽከረከርበት አንድ ዛቢያ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ሕይወት
ለእርሱ ክርስቶስ ነው። ከእርሱ ውጪ ሕይወት የለም። ለጳውሎስ መኖር
ማለት ክርስቶስ ነበረ። ለብዙዎች ምናልባት ሕይወት ዝናና ሥልጣን፥
ክብርና ሞገስ፥ ድሎትና ምቾት፥ አዱኛና ንዋይ፥ ሌሎችም ሊሆኑ
ይችላሉ። ለእኛስ?
ጳውሎስ ሞትንም ጥቅም ነው አለ። ሞትን ጥቅም ነው ማለት የሚችል
በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን ጌታ ያወቀ ሰው ብቻ ነው። ሞት
ለክርስቲያን የሚያስፈራ የንግግር ርእስ አይደለም። አንድ ጊዜ ብቻ
የተወለደ ሰው ሁለቴ ይሞታል፤ በሥጋም በዘላለማዊ ሞትም። ዳግም
የተወለደ ሰው ግን አንድ ጊዜ ብቻ ነው የሚሞተው። ክርስቲያን ሞትን
የማይፈራው የሞት መውጊያ የተወሰደለት በመሆኑ ነው፤ 1ቆሮ. በሙሉ፥
በተለይም 15፥20 እና 55-56። ጳውሎስ ከታሰረበት ተፈትቶ ቢለቀቅ
ወይም ተጠርቶ ቢገደል ለሁለቱም ዝግጁ ነው። ተርፎ ቢያገለግል ፍሬው
ይበዛል፤ ሞት ተፈርዶበት ከዚህች ምድር ቢሰናበት ወደ ተሻለው ስፍራ
ይሄዳል። በዚያ ስቃይም፥ መከራም፥ እስራትም፥ ግርፋትም፥ በተለይም
ኃጢአትም፥ ሰይጣንም የሉም። ለጳውሎስ ሞት ጥቅም ነበረ። ለእኛስ?
22-26፤ ነገር ግን በስጋ መኖር ለእኔ የሥራ ፍሬ ቢሆን፥ ምን እንድመርጥ
ኣላስታውቅም። በእነዚህም በሁለቱ እጨነቃለሁ፤ ልሄድ ከክርስቶስም
ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤ ነገር ግን
በሥጋ መኖሬ ስለ እናንተ እጅግ የሚያስፈልግ ነው። ይህንንም ተረድቼ፥
በእናንተ ዘንድ እንደ ገና ስለ መሆኔ፥ በእኔ መመካታችሁ በክርስቶስ
ኢየሱስ ይበዛ ዘንድ፥ በእምነት ታድጉና ደስ ይላችሁ ዘንድ እንድኖር
ከሁላችሁም ጋር እንድቈይ አውቃለሁ።
ይህ ማለት ለመኖር ወይም ለመሞት ጳውሎስ የምርጫ ነጻነት አለው
ማለት አይደለም። ይህ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንጂ የሰው ምርጫ
አይደለም። ይልቅስ ጳውሎስ እኛ ልቡን እንድናነብብና እንድናውቅ
ከፍቶ እያሳየን ያለ ነው የሚመስለው። ለማንም አገልጋይ፥ በተለይም
እንደ ጳውሎስ ላለ ራሱን ሳይቆጥብ፥ ለሰውነቱ ሳይሳሳ ለሚያገለግል
ሰው በሕይወት መቆየት በረከት ነው። ጌታ ይከብራል፤ ነፍሳት ይድናሉ፤
ቤተ ክርስቲያንም ትታነጻለች። ለጳውሎስ መሞትም መኖርም ሁለቱም
ትርጉም አላቸው። ሁለቱም እኩል ናቸው። ሁለቱም መፈታት ናቸው።
እንዲያው በሥጋ መፈታትን የሰፋና የነጻነት አገልግሎት አድርገን
ከቆጠርነው እንጂ ታሥሮም እያገለገለ ነው ይህን የጻፈው። ስለዚህ
ሁለቱም ለእርሱ መፈታት ናቸው። ይህ ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር
የሚለው መሄድ (ἀναλῦσαι አናሉሳይ) መፈታት፥ መለቀቅ
እንደማለትም ነው። እርግጥም ወደ ጌታ መሄድ መለቀቅ ነው። ወደ ጌታ
መሄድ ልክ ሥጋ ከወኅኒ እንደሚወጣው መፈታት ብቻ ሳይሆን ከዚያም
በላይ መለቀቅ ነው።
ጳውሎስ ቢኖር ለምን እንደሚኖር ጠንቅቆ የተረዳ ሰው ነው። ሞትም
ምን መሆኑን ፈጽሞ ያወቀ ሰው ነው። መኖሩ፥ መፈታቱና ማገልገሉ
ለቅዱሳን በጣም አስፈላጊ ነው። መሞቱም ጥቅሙ ነው። በሁለቱም
ጌታን ማክበርን ሊያከብርበት ሁሌም ስንዱ ሆኖ የኖረ ሰው ነው።
ለሚሞትለት ዓላማ የኖረ፤ ለኖረለት ዓላማም ሊሞት ቆርጦና ዝግጁ ሆኖ
የኖረ አገልጋይ ነው። እኛስ እንዴት ነን? ለምንኖርለት ለመሞት፥
ለምንሞትለትም ለመኖር የቆረጥን ነን?

2014 ጁን 23, ሰኞ

የዮናታን ተስፋዬ ገፅ: ቲ. ቢ. ጆሹዋ ማን ነው?ወዳጆች ሆይ፥ መንፈስን ሁሉ አትመኑ፥ ነገር ግን መና...

የዮናታን ተስፋዬ ገፅ: ቲ. ቢ. ጆሹዋ ማን ነው?
ወዳጆች ሆይ፥ መንፈስን ሁሉ አትመኑ፥ ነገር ግን መና...
: ቲ. ቢ. ጆሹዋ ማን ነው? ወዳጆች ሆይ፥ መንፈስን ሁሉ አትመኑ፥ ነገር ግን መናፍስት ከእግዚአብሔር ሆነው እንደ ሆነ መርምሩ፤ ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያት ወደ ዓለም ወጥተዋልና። 1ዮሐ. 4፥1 በ1ኛው የዓለም ጦርነት...
ቲ. ቢ. ጆሹዋ ማን ነው?
ወዳጆች ሆይ፥ መንፈስን ሁሉ አትመኑ፥ ነገር ግን መናፍስት
ከእግዚአብሔር ሆነው እንደ ሆነ መርምሩ፤ ብዙዎች ሐሰተኞች
ነቢያት ወደ ዓለም ወጥተዋልና።
1ዮሐ. 4፥1
በ1ኛው የዓለም ጦርነት መጨረሻ ላይ በቬርሳይ ስምምነት መሠረት
የጀርመንን ተላላፊነት ለመቅጣት ከግዛቷ ጥቂት በፈረንሳይ ተቆጣጣሪነት
ስር ሆኖ፥ ለጦርነቱ ውድመት ካሳ እንድትከፍል ተገድዳ፥ ለመከላከል
ብቻ የተወሰነ የጦር መሣሪያ ከማምረት በቀር ከዚያ ያለፈ እንዳታመርት
ታግዳ፥ የባሕር ኃይሏ የተወሰነ ገደብ ተደርጎበት የአየር ኃይል ጨርሶ
እንዳይኖራት ተደርጋ በማዕቀቡ ውስጥ ከአሥር በላይ ያህል የተዋረዱ
ዓመታት አሳለፈች። ከዚያ በኋላ ግን ሂትለር ተነሣና ሁሉንም
ተረማመደበት፤ በመጀመሪያ የባሕሩንም የተከለከለውን የአየሩንም የጦር
መሣሪያ ጡንቻውን ካፈረጠመ በኋላ በቀጥታ በፈረንሳይ ቁጥጥር ስር
የነበረውን የራይንላንድ ግዛት በጀርመን ጦር ገጠገጠበት። ከጃፓን እና
ከጣሊያን ጋር ግንባር በመፍጠር አውሮጳን ብቻ ሳይሆን ዓለምንም
ለመግዛት ወረራው ተጀመረ። 2ኛው የዓለም ጦነት የተጀመረው ጀርመን
በመጀመሪያ የወረራ እርምጃ ከቼኮዝሎቫኪያ ውስጥ ሱዴተንላንድ
የተባለውን ግዛት ስትይዝ ነው። ሁኔታው ያሳሰባቸው መሪዎች
የፈረንሳዩ ዳላዲዬር፥ የጣሊያኑ ሙሶሊኒ፥ እና የእንግሊዙ ቻምበርሌይን
ሂትለርን አነጋገሩት። ሂትለርም አሁን ከያዘው እንደማያልፍና ያንን
የያዘውም በአብላጫው የጀርመኖች መኖሪያ ስለሆነ ነው ብሎ
አረጋጋቸው። መሪዎቹም እንደዚያ ከሆነ የያዝከውን ልቀቅ አንልህም ግን
ከያዝከው እንዳታልፍ ብለው ወደያገራቸው ተመልሰው ሂትለር
እንደሚሰማውና እንደሚታየው ወራሪ አለመሆኑንና ከያዘው የማያልፍ
መሆኑን በመናገር ሕዝባቸው አረጋጉ። ይህ በዘመኑ Policy of
Appeasement ተብሎ የታወቀው ስሕተት ነበረ።
አሳቡ በለስላሳው ሲተረጎም አይቶ ዝም ማለት፥ አይቶ እንዳላዩ መሆን፥
መርካት፥ ማስደሰት፥ አለማስቆጣት፥ ቦታ መልቀቅ፥ ፈቀቅ ማለት፥
ሌላውን ለማስደሰት ዝም ማለት፥ ራስ እስካልተነኩ ለሌላው ደንታቢስ
መሆን ማለት ነው።
የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ኔቪል ቻምበርሌይን ይህንን ለአገሩ ሰዎች
በመስከረም መጨረሻ 1938 በሬድዮ ሲናገር፥ “እሩቅ አገር ያሉ ሁለት
የማናውቃቸው ሕዝቦች እርስ በርሳቸው ስለተዋጉ እኛ ምሽግ እየቆፈርንና
የመርዝ ጋዝ መከላከያ ጭምብል እየለካን የምናደርገው ይህ አሳፋሪ ነገር
ምንድርነው?” ብሎ ነበር። ያኔ የፓርላማ ተመራጭና ኋላ የጦርነቱ
ዘመናት ጠቅላይ ሚኒስትር የሆነው ዊንስተን ቸርቺል ይህን ሲሰማ
እንዲህ አለ፥ An appeaser is someone who feeds a crocodile
hoping it will eat him last. የመሪዎቹን ስምምነት በመንቀፍም፥ The
choice they made was between war and dishonour. They
chose dishonour; they will have war!” አለ። እውነትም፥ አስደሳችና
የማያስቆጣ ሰው ዐዞው ራሱን እስኪበላው ድረስ ጊዜ ለመግዛት ዐዞውን
የሚቀልብ ሰው ማለት ነው። መበላት ካልቀረ ማብላት ጠቀሜታው
ምንድርነው? እውነትም፥ ለማስደሰትና ላለማስቆጣት ብለው ከጦርነት
ይልቅ ዝምታን መምረጣቸው ውርደትን መምረጣቸው ነበር ጦርነቱ
አልቀረላቸውምና ሁለቱንም አገኙት። ቀድሞ ዝም ባይባል ለውጥ
ሊፈጠርና 2ኛው የዓለም ጦርነት ላይከሰትና ከ60 ሚሊዮን በላይ ሰዎች
ላያልቁ ይችል ነበር። ዝም የማይባሉ ጉዳዮች ላይ ዝም ማለት ጉዳትና
ውርደትን ከጦርነት ጋር መጥራት ነውና ዝም ማለት ተገቢ አይደለም።
ስለ ቲ. ቢ. ጆሹዋ መጀመሪያ ያነበብኩት ከ3 ዓመታት በፊት አንድ
የተወደደ የመዝሙርና አምልኮ አገልጋይ ከአገር ቤት ስለዚህ ሰው
በጠየቀኝ ጊዜ ነው። ጥያቄውን ለመመለስ ስል ስለ ሰውየው መረጃዎችን
መፈለግ ነበረብኝ። በጊዜው በጥቂቱ የማውቀውን ጻፍኩለት። በቅርብም
ይኸው ጥያቄ እንደገና ስለመጣ አሁንም በጥቂቱ ልጽፍ እወዳለሁ።
ልብን የሚያውቅ እግዚአብሔር ብቻ በመሆኑ የሰዎችን ግፊትና
የልባቸውን ሁኔታ ሰዎች ማወቅ አይችሉም። ግን የሚታዩና የሚሰሙ
ነገሮችን ከቃሉ አንጻር መፈተሽ እንችላለን። መቻል ብቻ ሳይሆን ይህ
እንዲያውም ተግተን እንድናደርግ የሚጠበቅብን ነገር ነው።
ከላይ ያልኩትን እንደገና ይህን ልድገመው፤ ዝም የማይባሉ ጉዳዮች ላይ
ዝም ማለት ውርደትን ከጦርነት ጋር መጥራት ነውና ዝም ማለት ተገቢ
አይደለም። ከዓመታት በፊት መንፈስ ቅዱስና ካሪዝማዊ ቀውሶች የተሰኘ
መጽሐፌ ታትሞ ሲነበብ እንደ ናዳ የተለቀቁብኝ ትችቶችና ጥያቄዎች
ነበሩ። ቢሮው ከኔ ቢሮ ሁለት በር ብቻ የሚርቅ አንድ አብሮኝ ይሠራ
የነበረ የኔው መሥሪያ ቤት ሰው፥ “ስለማታውቀው ነገር እንዴት
ትጽፋለህ? ለምሳሌ፥ ለመሆኑ በልሳን ተናግረህ ታውቃለህ?” አለኝ።
መጽሐፉ እንደጎመዘዘው ሁሉ መልሴም አልጣመውም። ስለ ሰይጣን
ለመጻፍ ሰይጣናም ወይም ስለ በሽታ ለመጻፍ በሽተኛ መሆን የግድ
የለብንም። ከመሠረቱ የዚህ ሰው መንደርደሪያው የተሳሳተ ነበረ። እንደ
እርሱ አስተያየት አንድ ሰው ስለ አንድ ነገር በግሉ ተለማምዶ
የሚናገረው ነገር (ለምሳሌ፥ እንደ እርሱ ጥያቄ በልሳኖች መናገር)
መጽሐፍ ቅዱስ ከሚለውም የበለጠ ሥልጣን አለው የሚል ነው።
ስሕተቱ ሰብዓዊና ኅሊናዊ ልምምድን ከነባራዊው ቃሉ በላይ ካደረግን
ውርደትና ውድቀትን መጋበዛችን መሆኑ ነው።
በጣም ሃይማኖተኛ በሆነ ሕዝብ መካከል ስለምንኖር ድንቆች
ምልክቶችና ተአምራት ሃይማኖተኛነታችንን ያጎለብቱልናል ብለን
እንድንቀበል አስተዳደጋችን ይሞግተናል። በአገራችን ከልማዳዊ
አስተዳደጋችን ስናውቅ ጠንቋዮች፥ ባህታውያን፥ ደብተራዎች፥ ቃልቻዎች
15
ቁጥር 􀅧􀆅 - ግንቦት ፪ሺህ ፭ ezralit@gmail.com ዓመተ ምሕረት MAY 2013
ምልክት ያደርጋሉ። ሰዎቹ ብቻ ሳይሆኑ ቦታዎችም (ይህ ጠበል፥ ያ
ደብር፥ ይህ ዛፍ፥ ያ ወንዝ)፤ ዕቃዎችም (ውኃው፥ እመቱ፥ ጥፈቱ፥
ጠጠሩ)፤ ድርጊቶችም (ጦሱ፥ እርግማኑ፥ ጥላው፥ ቡዳው) ወዘተ፥
የራሳቸው ውስጣዊ ተአምራዊ ኃይል ያላቸው አድርገን በመውሰድ
ስላደግን ይህ ሃይማኖታዊ ተጋቦት ወደ ክርስትና ስንመጣም (በተለይ
ከሃይማኖታዊ ዳራ ለመጣን) ከተጻፈው እውነት የበለጠ ምልክታዊው
እንቅስቃሴ እንዲማርከን ይጠራናል። አንዳንድ ሰዎች ገር ይመስላሉ፤ ገር
ሊሆኑም ይችላሉ። ገርነት ግን የትክክለኛነት መለኪያ አይደለም።
እውነተኛ አድርገው ራሳቸውን የሚቆጥሩ ሰዎች ፍጹም ስሕተት ውስጥ
ሊገኙ ይችላሉ። ስሕተትን ሊያስተውላት የቻለ ሰው የተባረከ ነው።
መመርመርና መጠየቅ
የሚታይ ድንቅ ተአምር ወይም ፈውስ እና መንፈስን መመርመር
ለምርጫ ቢቀርቡላቸው ተአምሩን ያለምንም ጥርጥር የሚመርጡ ለስላሳ
ክርስቲያኖች አሉ። እነዚህ ተአምራቱን ሰይጣንም ቢያደርግ ለመቀበልና
ሁል ጊዜ ለመወናበድ የተዘጋጁ ሰዎች ናቸው። መንፈስን መመርመር
የእግዚአብሔር ቃል ሳይሆን ጭራሹኑ ኃጢአተኝነት የሚመስላቸውም
አሉ። እነዚህ ተአምራትን ሲያዩ ያለ ጥርጥር የሚወስዱ
የሚቀርብላቸውን ሁሉ ሳይጠይቁ የሚበሉና ከዚያ በኋላ ለማስታወክ
የሚከጅላቸው ናቸው። አንድ ቀን አንድ ጓደኛዬ ጓደኛውን ወደ አንድ
ምግብ ቤት ወስዶ ከጋበዘው፥ ተጋባዡም በሳህኑ ላይ ምንም
እስከማይተርፍ በደስታ ከበላና ከጨረሰ በኋላ የበላው የእንቁራሪት ሥጋ
መሆኑን ነገረው። ለአንዳንድ አገር ሰዎች ይህን መብላት ማለት ለአበሻ
የዶሮ ሥጋ ወጥ እንደመብላት ያህል ነው። ይህ ተጋባዥ ግን ፈረንሳዊ
ሳይሆን አበሻ ነውና ከልቡ ነበር ያዘነው።
በ1ዮሐ. 4፥1 መናፍስትን ስለመመርመር ያለው መመርመር (δοκιμάζω
ዶኪማዞ) የሚለው ቃል መፈተሽ፥ መፈተን፥ ማረጋገጥ፥ ማጣራት ማለት
ነው። የሚጣራና የሚፈተሽ ነገር ያንን የሚመስል ግን ያንን ያልሆነ ነገር
በመኖሩ ነው። እግዚአብሔር ተአምራትን የሚያደርግ አምላክ ነው፤ ይህ
የአምላክነቱ አንድ መታወቂያ ነው። ግን እግዚአብሔር ብቻ አይደለም
ተአምራትን የሚያደርገው፤ አስመስሎ ተአምራትን የሚያደርግ ሌላ አለ።
እርሱም ሰይጣን ነው። ሰይጣን ተአምራትን ሲያደርግ የራሱን ሰዎች
በጉያው ለመጠበቅና በቁጥጥሩ ስር ለማቆየት ሲል ሊሆን ይችላል።
ወይም ያመኑትን ከማመን ለማሳት ሊያደርግ ይችላል። ራእ. 13፥13-14
አውሬው አሳች ምልክቶችን እንደሚያደርግ ይናገራል። ጌታም
በመጨረሻው ዘመን በስሙ ስለሚመጡ አሳቾች ይናገራል፤ ማቴ.
24፥24፤ ማር. 13፥22። በስሙ መምጣት እኔ እርሱ ነኝ ብሎ
መምጣትም፥ የሚያደርገውን ነገር በእርሱ እንደተደረገ ለማስመሰል
በስሙ ማድረግም ሊሆን ይችላል። ሰይጣን በሚያደርጋቸው ተአምራት
የሚያምኑትንና የተመረጡትንም እንኳ እስኪያስት ድረስ መሆኑ
ተጽፎልናል። ስለዚህ ተአምራትን ቁርበታቸውን ብቻ ሣይሆን ሥጋና
አጥንታቸውንም ጭምር መመርመር አለብን።
ወደ ቲ. ቢ. ጆሹዋ ልመለስ። በዚህ መጣጥፍ ስለዚህ ሰው ብቻ ሳይሆን
ይህን የሚመስሉ አገልግሎቶች ስላሉአቸው ሰዎች አመልካች ነገሮችን
ወይም ጠቋሚ ነጥቦችን ማስተላለፍ እፈልጋለሁ። በዚህ መጣጥፍ
ውስጥ ያካተትኳቸው ስምንት ነጥቦች የሚከተሉት ናቸው፤ 1) ራሴ
ከአካባቢዬም ካሉ ሌሎች ከሰማሁትና ከመረጃ መረብ ካየሁት፤ 2)
የአገሩ ሰዎች ምስክርነት፤ 3) ከውስጡ የወጡ ምስክርነት፤ 4) የፍተሻ
(screening) ጥያቄ፤ 5) የውሸታም ፈውሶች ጥያቄ፤ 6) የተአምራት
ምንነት ጥያቄ፤ 7) እንግዳ ጥንቆላዊ አሠራሮች ጥያቄ፤ 8) የትንቢት
ዓላማ ጥያቄ።
1) ካየሁት፥ ከሰማሁት፥ ከጠየቅኩት
የቲ. ቢ.ን የቪዲዮ መልእክቶች የተወሰኑ ተመልክቻለሁ። በጥቂት ብቻ
መፈረጅ ቢከብድም በጥቂት ብቻ ሳይሆን ከዚያ ባነሰም መፈተሽ
ይቻላል። ከሰማኋቸው መካከል ግን ያለጥያቄ፥ ‘እውነት ቃሉ ያንን
ይላል?’ ሳልል የሰማኋቸው የሉም። ከጠየቅኳቸው ደግሞ ይህ ሰው
በክርስቲያኖችም ክብ ውስጥ አንዳንዶች የዘመናችን ታላቅ ነቢይና
የእግዚአብሔር ሰው ሲሉት ሌሎች ሰይጣናዊ ሥራዎችን በመሥራት
የተካነ ሐሰተኛ ነቢይና አሳች አድርገው ያቀርቡታል። አናሳ ምርምር
ለማድረግ ከማውቃቸው ጥቂት ሰዎችን በመጠየቅ ነው የጀመርኩት።
ከፊሉ ፈጽሞ አያውቁትም። የሚያውቁቱ ደግሞ ዝንጉርጉር ናቸው።
ከላይ እንዳልኩት የእግዚአብሔር እጅ ነው የሚሉ አሉ። ፈጽሞ የሳተና
የሚያስት ሰው ነው የሚሉም አሉ። ማስረጃ ስጠይቅ ደጋፊዎቹ
የYouTube ምስሎችን ብቻ የሚጠቅሱ ሲሆኑ ከዚያ ያለፈ ምንም
ያላደረጉ ናቸው።
ከነቃፊዎቹም ጥቂቱ ከYouTube ምስሎች ብዙም ርቀው አልሄዱም።
ጥቂቱ ግን እንዲያው ማየት ብቻ ሳይሆን ለእይታና ለመስኅብነት
ተብለው የተቀነባበሩ ነገሮች እንደሚታዩበት ተጠንቅቀው ያዩና
ያስተዋሉም ናቸው። ደግሞም እነዚህን ነገሮች የሚያጋልጡ ሌሎች
የቪድዮ ቁራጮችንም ማየታቸውንም ጠቅሰው ሌሎችንም
የሚያስጠነቅቁ ሆነዋል። የዘመናችን ትልቅ መረጃ አቀባይ YouTube
መሆኑ ቢያስገርምም ከተገኙ ነገሮች መነሣቱ የግድ ነው። የቴሌቪዥን
ስርጭቱ በኢትዮጵያ በብዙዎች ዘንድ የሚታይ መሆኑ ይሰማል። ስለዚህ
በአገራችን ሰዎች ዘንድም መታወቁና ተቀባይነቱ ወይም ጠያቂ በሆኑት
ዘንድ መመርመሩ ተመሳሳይ ሳይሆን አይቀርም ብዬ እገምታለሁ።
በአገራችን በአማካዩ ምእመን ዘንድ ስም አንድ ጊዜ ጣራ በስቶ ከወጣ
በኋላ የባለስሙ ማዕረግና ዝና እንጂ ትምህርቱ ላይ ትኩረት
አይደረግም። ያ ስሙ የገነነ ሰው የሚሳሳት ከቶም አይመስልም።
የመመርመርና ይህ ነገር ወይም ይህ ትምህርት ከቃሉ ጋር ይስማማል
ወይስ ይጋጫል ብሎ መጠየቅ የሚያስፈልገው ለራስም ለሌሎችም
ጤንነት ነው።
መጽሐፍ ቅዱስ እውነትን ከስሕተት ለይተን የምናበጥርበት
ማበጠሪያችንም ነውና መጽሐፍ ቅዱስ የማይለውን እያስተማረና እያደረገ
ያለ ሰውን ክርስቲያን ነው ማለት እንዴት ይቻላል? ትምህርቱ ነው ወይስ
ልምምዱና ድርጊቱ ነው መለኪያው? በዚህ ዘመን የቤተ ክርስቲያንን
ጉልበት እንደብል እየበላ ያለው አንድ ትልቅ ስሕተት በአእምሮ ማሰብን
ትቶ በስሜት ማሰብ ነው። ስሜት ደግሞ ማሰቢያ አይደለምና
አያስብም። የሚሰብኩና የሚያስተምሩም ቃሉን ለሰዎች አእምሮ እንጂ
ለስሜታቸው አይናገሩም፤ ለስሜት ብቻ መናገርም ተገቢ አይደለም።
ጭንቅላትን በመደርደሪያ ላይ አስቀምጦ ከመደርደሪያው ላይ መጽሐፍ
ቅዱስን ወስዶ ማንበብ አይቻልም። ወይም ጭንቅላትን እቤተ ክርስቲያን
ደጃፍ ላይ እንደ ካቦርት ሰቅሎ ገብቶ ማሰብ አቁሞ፥ አምልኮ በሚመስል
ስሜት ሲዋከቡ ቆይቶ ሲወጡ እንደገና ሰክቶ መውጣት ጥበብ
አይደለም። ቤተ ክርስቲያን የአእምሮ መካነ መቃብር አይደለችም።
ስለዚህ ማንንምና ምንንም ከመጽሐፍ ቅዱስ አንጻር መጠየቅና
16
ቁጥር 􀅧􀆅 - ግንቦት ፪ሺህ ፭ ezralit@gmail.com ዓመተ ምሕረት MAY 2013
መመርመር ተገቢ ብቻ ሳይሆን የግዴታ ጉዳይ ነው።
2) የአገሩ ሰዎች ምስክርነት
የቅርቦቹ ያውቁታልና ከገዛ አገሩ ሰዎች ልቀጥል ብዬ የናይጄሪያ አብያተ
ክርስቲያናት ስለ እርሱና ስለ አገልግሎቱ ያላቸውን ማንበብ ፈለግኩ።
ያስገረመኝ የናይጄሪያ አብያተ ክርስቲያናት በጠቅላላው፥ ምልክቶችና
ተአምራት ላይ የሚያተኩሩት ጴንጤቆስጣውያኑም ሳይቀሩ፥
የማይቀበሉት ብቻ ሳይሆን የሚያወግዙትና የሚያማርሩበት ሰው ነው።
ቲ. ቢ. የናይጄሪያ ጴንጤቆስጣውያን ማኅበር (PFN) በግልጽ ያወገዘው
ሰው ነው። አንድ ሰው እንዳለው፥ “እና ምን ይጠበስ? ነቢይ በገዛ አገሩ
ባይከበር ምን ያስገርማል” ማለት ይቻል ይሆናል። እንዲያስገርም
የሚያደርገው ልዩነት ግን ያንን የናዝሬቱን ነቢይ ያልተቀበሉት ሰው ብቻ
የመሰላቸውና የተሰናከሉበት አይሁድ ሲሆኑ እነዚህ ግን የዚያ የናዝሬቱ
ነቢይ የክርስቶስ ተከታዮች ናቸው። ይህች ቤተ ክርስቲያን ናት።
የወንጌላዊ ቦንኬ አገልግሎት የሆነው CFAN በናይጄሪያ ብዙ የጀማ
ስብከቶችን አካሂዶአል። የCFAN ምክትል ፕሬዘደንት Peter
Vandenberg ከዓመታት በፊት በናይጄሪያ ስለነበረው አገልግሎት
ሲናገር፥ ከ2000 የሚበዙ የናይጄሪያ አብያተ ክርስቲያናት በተሳተፉበት
በናይጄሪያ ባደረጓቸው ጉባኤዎች ሁሉም አብያተ ክርስቲያናት ቲ. ቢ.ን
ማውገዛቸውን፥ የሚሠራቸው ሥራዎች ምንም በኢየሱስ ስም ቢሆኑ
መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆኑንና በናይጄሪያ በሰፊው ከተለመዱ የጥንቆላ
አሠራሮች ጋር የተያያዙ እንደሆኑ መናገራቸውን ጠቅሶአል። ከዚህ የተነሣ
CFAN በናይጄሪያ ከቲ. ቢ. ጋር እንደማይሠራ ገልጦ፥ “በናይጄሪያ ያሉት
ወንድሞቻችን በዚያ ምድር የሚኖሩ ናቸውና ከኛ ይበልጥ ስለጉዳዩ
እነርሱ ያውቃሉ።” ብሎአል።12
በሌጎስ የቤተ ክርስቲያን ቄስ የሆነው Chris Okotie ቲ. ቢ. ጆሹዋ
ድብቅና ምስጢራዊ አሠራሮቹ መወገዝ ያለባቸው በቀላሉ የሚታመን
አጭበርባሪ (charlatan) ሰው ነው” ሲል Joseph Thompson የተባለ
የናይጄሪያ የወንጌል አገልጋይ፥ “ቲ. ቢ. ጆሹዋ በናይጄሪያም ሆነ
በጠቅላላው ዓለም ላለችው ለክርስቶስ አካል አደገኛ ሰው ነው” ብሏል።13
እነዚህ ሰዎች ደጋግመው የሚጠቅሱት ቲ. ቢ. በኢየሱስ ስም ቢጸልይም
በመጽሐፍ ቅዱስ ከቶ ያልተደረገ ክርስትናን ከጥንቆላ ጋር የመበረዝ
ድፍረት እንደሚታይበት ነው። እነዚህ ሰዎች ይህን ሰው በቅርብ
የሚያውቁ የአገሬው ሰዎች ናቸው።
3) ከውስጡ የወጡ ሰዎች ምስክርነት
ምናልባት የገዛ አገሩ ሰዎች ያልተቀበሉት ነቢይ በውጪዎቹ ባይከበርም
የውስጦቹ ያደንቁታል ተብሎ ይታሰብ ይሆናል። ከውስጡ የወጡ ሰዎች
የሚሉትን መስማትም ሌላ የእይታ አቅጣጫን ሊሰጠን ይችላል።
ቢሶላ ጆንሰን (Bisola Johnson) ያወጣችው Deception of the Age
ዲቪዲ የሰውየውንና የምኩራቡን አሠራር ያጋለጠ ነው። ይህንን ዲቪዲ
12 http://www.toetsalles.nl/htmldoc/bio.joshua.charisma2.htm
13 http://www.nigeriavillagesquare.com/articles/sunnychris-
okenwa/tb-joshua-a-false-prophet-in-thesynagogue.
html
ከYouTube በርእሱ ማየት ይቻላል። በዚህ
ዲቪዲ የሚመሰክረው Agomoh Paul ሌላው
የቲ. ቢ. ደቀ መዝሙርና የጋና ወኪሉ የነበረ
አገልጋይ ነው። ስሞቻቸውን በተጻፉበት አጻጻፍ
ያስቀመጥኩት ሲተረጎም የአጠራር ግድፈት
እንዳይኖር ነው። Agomoh ከ10 ዓመታት
የምኩራቡ አገልጋይነት በኋላ ነው ተለይቶ
የወጣው። እነዚህ የሰውየውን ማንነት ብቻ
ሳይሆን በደቀ መዛሙርቱ ላይ የሚደረገውን
አካላዊ፥ ስነ ልቡናዊና መንፈሳዊ ጫናም ያጋለጡ
ከቲ. ቢ. ተለይተው ከመውጣታቸው በፊት ደቀ
መዛሙርቱና አብረውት አገልጋዮቹ የነበሩ ሰዎች ናቸው።
እነዚህ ምስክሮች ውሸታሞች ናቸው የሚል ምላሽ ከምኩራቡ ተዘጋጅቶ
ተበትኖአል። ይህንንም ተመልክቼአለሁ። በነዚህ ላይ የተሰጠው
የምኩራቡ ምላሽ ከቀድሞ የተጠራቀሙ ቴፖችን በማውጣት እነዚህ
አጋላጮች ሳይሆኑ አላጋጮች መሆናቸውን፥ ቀድሞ እንዴት ያሉ
ምስኪኖች መሆናቸውንና ይህንን ያደረጉት ለጥቅማቸው ብቻ ሲሉ
እንደሆነ ተደርጎ ነው። የቴፖቹ መውጣት ከቀደመ ምስክርነታቸው
ተወስዶና ተቀነባብሮ መሆኑ ምላሹ መስካሪዎቹን ውድቅ ለማድረግ
የታለመ ነው። ይሁን እንጂ ለጥቅም ብለው አደረጉ ከተባለና እውነትም
ይህን ያደረጉት ለጥቅም ከሆነ ይህን ያስደረጋቸው ጥቅም ምንነትና
የአስደራጊው ማንነት መደበቅ አልነበረበትም። ምስጢራትን ከሚያውቅ
ነቢይ ነኝ ከሚል ሰው ይህ መሰወር የለበትም። ወይስ ላለመበቀል
በይቅርታ ለማለፍ ነው? ከሆነ የሚያሳጣው የቀድሞ ምስክርነታቸው
በሚገርም ሁኔታ ተቀነባብሮ ለምን ወጣ?
ቢሶላ ከመውጣቷ በፊት የምኩራቡ የሚዲያ ቡድን አቀነባባሪና ኃላፊ
ናት። የሚደረገውን የቪዲዮ ቅንብር አሳምራ ስለምታውቅ ይደረግ
የነበረውን በግልጽ ተናግራለች። ይህ ሐሰት ቢሆን የሚያስከስስ ነው።
ያጋለጡት ነገሮች አጋላጮቹ በውሸት አድርገውት ቢሆን ስም ማጉደፍ
ነውና በአገሪቱ ሕግ የሚያስከስሱ ቢሆኑም የክስ ፋይል
አልተከፈተባቸውም። ለምን? በአንጻሩ የተናገሩአቸው ነገሮች እርሱንም
የሚያስጠይቁና የሚያስከስሱ ወንጀሎች ናቸው። አልተከሰሰም። ለምን?
ምናልባት በአገሪቱ የግብረ ገብነት እንጂ የሕግ መተላለፍ አይደሉ ይሆን?
የሚሉና የመሰሉ ጥያቄዎች ሊነሱ ይችላሉ።
እነዚህ ሰዎች የሚናገሩአቸውን ነገሮች የሚያውቁ የውስጥ ሰዎች ናቸው
እንጂ ያሉትን ቃል የተናገሩት ከውጪ መርምረውና ለቅመው አይደለም።
Nii Ayiku Amartey የተባለ የቲ. ቢ. የጋና አጋሩ የነበረ አገልጋይ ስለ
ጋናው አገልግሎት አጀማመር ሲናገር፥ “ቲ. ቢ. ጆሹዋ በ20 ሰዎች አካባቢ
በተቀናበሩ ተአምራት የጋናን ሰዎች አስቶ ነበር የገባው። ያኔ ተፈወሱ
የተባሉት የተአምራት ተቀባዮች ዛሬ 20ዎቹም ሰዎች በሕይወት የሉም።”
ብሏል።
ሌላው የቲ. ቢ. የጋና ወኪል አገልጋይ የነበረው
Pastor Peter Kayode የተባለ ሰው ቲ. ቢ.
እንዴት አድርጎ ሚስቴን እንደወሰደ በሚል ርእስ
በናይጄሪያ ታዋቂ የክርስቲያን መጽሔት
(Lifeway) በ2009 በዝርዝር ዘግቦአል። የPeter
Kayode ምስክርነት እንደ Paul Agomoh
ምስክርነት ቲ. ቢ. ትዳር በሚፈልጉና በባለትዳር
አገልጋዮች ላይ ያለውን ከመስመር የወጣና መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆነ
17
ቁጥር 􀅧􀆅 - ግንቦት ፪ሺህ ፭ ezralit@gmail.com ዓመተ ምሕረት MAY 2013
ሥልጣን ትዳር እንዳይመሠረት ብቻ ሳይሆን ለትዳር መፍረስም መሣሪያ
ያደርገዋል። ልጅ ስላልወለዱ እንዲጸለይላቸው ብሎ በሄደበት Lola
የተባለች ሚስቱን ቲ. ቢ. የምኩራቡ አገልጋይ ሆና እዚያ እንድትቆይና
ከባሏ እንድትለይ አድርጎ ባሏ Peter Kayode ከእርሷ እንዳይገናኝ ብቻ
ሳይሆን ርቆ ወደ ጋና ለአገልግሎት እንዲሄድ በመላኩ የደረሰው የ5
ዓመት መለያየትና የትዳር መናጋት ብቻ ሳይሆን ከገዛ ቤተሰቡ ጋር
በቁርጥ መለያየቱም ጭምር ነው። የሆነበትና የደረሰበት ሁሉ በግልጽ
የታየውና ከቲ. ቢ. ምኩራብ ለመለየት የቆረጠው የአባቱ ቀብር ላይ ሳለ
ነበር።14 ልጅ የሚሹ ባልና ሚስት መለያየት ጭራሽ ልጅ እንዳይኖራቸው
ዕድሉን ማበላሸት አይደለም ወይ? እንዴት ነው ተለያይተው ልጅ
ሊኖራቸው የሚችለው? ችግሩ ግን ከዚህም ያለፈ ነበር።
የዚህን ሰው አሳዛኝ ሁኔታና Lola ከቲ. ቢ. ጋር ስለነበራት ሁኔታ
Agomohም ተናግሮአል። ባሏ ከሚስቱ ተለይቶ በጋና በቆየባቸው
አምስት ዓመታት ውስጥ Lola አርግዛ እንደነበርና ማርገዟ ሲታወቅ ወደ
ባሏ ወደ ጋና እንደላካት (ዳዊት ቤርሳቤህን አስረግዞ ኦርዮ ወደ ሚስቱ
እንዲገባ ለማድረግ እንደሞከረው መሆኑ ነው።) እና ኋላ ውርጃ
እንደተደረገም ተናግሮአል። የPeter Kayode ምስክርነት በጊዜው በጋና
አብሮት በነበረው በAgomoh የተደገፈና የተረጋገጠ ነው። እንዲያውም
Agomoh ስለሚወራው ወሬና ስለ ጉዳዩ ለቲ. ቢ. ሲያነሣበት እንዲረሳው
ነው የነገረው። የእነዚህን የሚመስል ምስክርነት ያላቸው እንደነ Nosa
Idumumonyi እና Francis Egharevha ያሉ ሌሎችም አሉ። ሁሉን
በዚህ አጭር መጣትፍ መጨረስ አይቻልም።
ይህ እንዲህ ያለ ጥያቄ እንድንጠይቅ ያስገድደናል። በአገልጋዮቻቸው ላይ
እንዲህ ያለ ጫና ማድረግ፥ ጋብቻን መከልከልና አለማበረታታት፥
የተጋቡትን አብሮ ከመሆን ማገድ፥ መቼ አብረው መሆን እንዳለባቸውና
እንደሌለባቸው ጊዜ መወሰን፥ ከቤተሰብ መለየትና ፍጹም በሆነ ቁጥጥር
ስር ማዋል ክርስቲያናዊ መሪነት ነው ወይስ የስሕተት አስተማሪዎች
(የcult leaders) አንድ ምልክት? እነዚህ ከውስጡ የወጡ ሰዎች
ምስክርነት የሰውየውን ስነ ምግባራዊ ሕይወት እጥያቄ ውስጥ የሚከትቱ
ብቻ ሳይሆኑ የሚያጋልጡም ናቸው። እዚህ ላይ የሰዎቹን ምስክርነትም
ሆነ ምኩራቡ ለክሱና ለማጋለጡ ምላሽ የሰጠውን የምስክርነቱን
ማጣጣያ መስማት ወይም ማየትና መፈተን የአንባቢ ኃላፊነት መሆኑን
ሳሳስብ ይህ የመፈተንና የመመርመር ተግባር በአገልጋዮች ሁሉ
ክርስቲያናዊ አመላለስና በትምህርቶቻቸው ላይ መደረግ እንዳለበት
በማለት ጭምር ነው። ከተነገሩት ነገሮች መካከል ከእኅትማማቾች ጋር
ግብረ ሥጋ መፈጸምን፥ በምኩራቡ የሚያገለግሉ ልጃገረዶችን ድንግልና
መገሰስንና ሳያገቡ ለ15 ዓመታትና ከዚያ በላይ እንዲቆዩ ማድረግን፥
በዝሙት ተከስሰው የመጡ ሴቶች ራቁታቸውን በደቀ መዛሙርት (ቅርብ
አገልጋዮቹ) ፊት መቅጣትን (ለምሳሌ፥ አንዷ ራቁቷን መጥታ በብልቷ
በርበሬ መጨመሩ) ይህንም የሚመስሉ ይገኙበታል። Agomoh
በምስክርነቱ ቪዲዮ ቲ. ቢ. ጆሹዋን የገለጠበት ቃል፥ “ይህ ሰው
የአሳችነት ሁሉ ቁንጮ ነው፤ እርሱ የማስፈራሮ ሁሉ ክምችት ነው”
የሚል ነው።
14 http://fortheloveofhistruth.com/2012/03/15/profit-ofdoom-
an-expose-on-t-b-joshua-of-the-synagogue-church-ofall-
nations-nigeria/
4) የፍተሻ (screening) ጥያቄ፤
ይህ ፍተሻ ወይም ጥሩ የሚመስለውን ጥሩ ከማይመስለው የማንገዋለል
ነገር እጩዎችን ለማግኘት የሚደረግ ሙከራ ነው። ይህ ማጣራት
በሽተኞችን የመጠየቅና የትኞቹ ለቴሌቪዥን ትዕይንት ይመቻሉ፥ የትኞቹ
መቅረብ የሌለባቸው ናቸው የሚለውን ለመለየት ብቻ ሳይሆን
የሚቀርቡቱና በቴሌቪዥን የሚቀረጹቱ ማድረግ ያለባቸው ነገሮች
በግልጽ ተነግሮአቸው ወደ መድረኩ የሚጠጉበት ሥርዓትም ነው።
ለምሳሌ፥ ተነሥተው መራመድ የሚችሉ ድኩማን በዊልቸር ተገፍተው
ይሄዱና ተነሥተው በተመልካች ፊት እንዲራመዱ ይደረጋሉ። Agomoh
የተጸለየላቸው ሰዎች መፈወሳቸውን እንዲመሰክሩ እንዴት
እንደሚያቀነባብሩና በዊልቸር የመጡ ሽባ ያልሆኑ ሰዎች ተቀምጠው
ቆይተው በመጨረሻ ተነስተው እንዲራመዱ እንደሚደረጉ በዚህ ድርጊት
ራሱም ዋና አስተባባሪና ተሳታፊ መሆኑን በግልጽ ተናግሮአል።
ከዓመታት በፊት በአሜሪካ ይደረጉ በነበሩት የፈውስ ጉባኤዎች
አስተናጋጆችና እንግዳ ተቀባዮች የማይታይ የድምጽ መቀበያ ማይክሮፎን
ተደርጎላቸው ወደ ጉባኤው የሚመጡ ታማሚዎችን ሲያናግሩ
ፈውሰኛው ሰው ከውስጥ ሆኖ በሬድዮ መገናኛ እየሰማ ኋላ
የታማሚዎቹን ሕመም ብቻ ሳይሆን የሰማውን ታሪካቸውንም እየዘከዘከ
ይናገርና ስነ ልቡናዊ ፈውስ ያድል ነበር። ይህ የዜና ማሰራጫዎች ሳይቀሩ
ያናፈሱት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ያጋለጡትም እነርሱው ናቸው።
ወደ ቲ. ቢ. ጉባኤ የሚሄዱ ጎብኚዎችና ሕሙማን የሚሞሉት ቅጽም
አለ። ታሪካቸውን የሚዘረዝሩበት ነው። ቅጹ የሆስፒታል ሜዲካል ቅጽ
ነው የሚመስለውም የሚያህለውም። ሕመማቸውና የሕመሙ ታሪክ፥
ጊዜውና ዘመኑ፥ የሚወስዱት መድኃኒት ሳይቀር ይዘረዘራል። ቅጹን
ከመረጃ መረብ ማየት ይቻላል። አንዳንዶች የሚከፈል ገንዘብ መኖሩን
ሲናገሩ ሌሎች የለም ገንዘብ አይከፈልበትም ይላሉ። ከቅጹ በተጨማሪ
ሰዎች ወደ ምኩራብ ለመግባት ገና ሳይነጋ ጀምሮ ወደ ምኩራብ
ለመግባት ተሰልፈው ሳሉ የመጡበትን ጉዳይና ምክንያት እየጠየቁና
እያጠናቀሩ የቲ. ቢ. የትንቢቱ መንደርደሪያ እንዲሆኑ አሰናድተው
እንደሚያቀርቧቸው የ Agomoh ምስክርነት ይገልጣል።
ይህን መሳይ አገልግሎት በፈውሰኞች አገልግሎት የተለመደ ነው።
የሚታዩ በሚልቸር የተቀመጡና በሸክም የመጡ ድውያን ተኮልኩለው
እነ እንቶኔ የሐሞት ከረጢትና የኩላሊት ጠጠር፥ የማኅጸንና የጣፊያ
ሕመም ብቻ ይጣራሉ። የቲ. ቢ.ን ዓይነት የማጣራት ሥራ በመጽሐፍ
ቅዱስ ውስጥ ከቶም ታይቶና ተሰምቶ አይታወቅም። በብሉይም ሆነ
በአዲስ ኪዳን ተአምራት ሲደረጉ ከጌታ ፈቃድና ከአስፈላጊነታቸው
ወይም ተፈላጊነታቸው እንጂ በሰዎች ቅንብርና አደራረግ አልነበረም።
ይህንን ከ Agomoh የምስክርነት ዲቪዲ የሰማሁትን በፈውስ ስፍራ
ተገኝተው ከነበሩ የማውቃቸው የቅርቤ ሰዎችም ሰምቼአለሁ። ይህ
እውነት መሆኑን እኔም አረጋግጣለሁ። ከጥቂት ወራት በፊት (በ2012
መጨረሻ ወራት) የቲ. ቢ. ወኪል የሆነ ሰው ወደ ሲያትል ዋሺንግተን
መጥቶ የፈውስ ዘመቻ አድርጎ ነበር። እነዚህ ወገኖች የሄዱት አካላዊ
ፈውስን ፈልገው ነው። በስፍራው የታዘቡት ግን አጎሞ የተናገረውን
ነው። መንቀሳቀስ የማይችሉቱ ወደ መድረኩም እንኳ እንዳይቀርቡ ካርድ
እየተሰጣቸውና አዳራሹም በመደብ በመደብ እየተከፈለ ራቅ ያለ ስፍራ
እንዲሆኑ ተደርገው ተመድበው ነበር። ከሁለቱ አንዱ እግሩን
የሚሸመቅቀው ወንድም በዊልቸር አይሄድም ግን በዊልቸር ተደርጎ ወደ
መድረኩ እንዲሄድና ሲጸለይለት እንዲራመድና እንዲታይ ተደግሶለት
18
ቁጥር 􀅧􀆅 - ግንቦት ፪ሺህ ፭ ezralit@gmail.com ዓመተ ምሕረት MAY 2013
ነበር። ይህ በነአጎሞ የተነገረውን ምስክርነት እውነትነት ያረጋገጠልኝ
አጋጣሚ ነው። ከላይ በተራ ቁጥር 1 ያደረግኩትን መጠይቅ ሳካሂድ
ከዚህም የከፋ ገጠመኝ ሰማሁ። በዚህ መጣጥፍ ልጽፈው የማልችለው
ይህ ገጠመኝ አሜሪካ ባለ አንድ ክርስቲያን ቤተሰብ ላይ የደረሰ ሲሆን
መንፈሳዊም፥ ስነ ልቡናዊም፥ አካላዊ ጉዳትም የደረሰበት ነው።
ይህን የፍተሻ አሠራር ከመጽሐፍ ቅዱስ አንጻር ስንመለከተው ለሐሰተኛ
ፈዋሾች የተሳሳተ አካሄድ የሚመች ብቻ ሳይሆን ሕመምተኞችን ግራ
የሚያጋባና እግዚአብሔርንም የሚንቅና የሚያሰድብ ድርጊት ነው።
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከቶም እንዲህ የመሰለ ነገር አልተጻፈም። ሰዎች
በቅጽበትም በሂደትም ተፈውሰዋል። ግን ምርጡን መፈወስና ምራጩን
መጣል ፈጽሞ አልታየም። ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ፥ በተለይም የአዲስ
ኪዳን አገልግሎት አይደለም።
5) የውሸታም ፈውሶች ጥያቄ፤
ቲ. ቢ. የፈውስ ስጦታን የተቀበለው ሲወለድ መሆኑን ተናግሮአል።
በአዲስ ኪዳን ተጽፎ የምናገኘው ደግሞ ስጦታዎች የተሰጡት አካሉን
ለማነጽ ለብልቶቹ መሆኑ ተጽፎአል፤ 1ቆሮ. 12፤ ኤፌ. 5፤ ሮሜ 12፤ 1ጴጥ.
5። ቲ. ቢ. እንደሚለው ስጦታ ከእናት ማኅጸን ስንወጣ የምናገኘው ከሆነ
ክርስቲያን ያልሆነም ሰው የፈውስ ምልክት ቢያደርግ፥ አባይ ጠንቋዩም
ምልክት ቢያሳይና በሽተኞች ቢፈወሱ ሰዎች፥ “ይህ ከእግዚአብሔር እንጂ
ሌላ ሊሆን አይችልም” እንዳይሉ ምን ያደርጋቸዋል? መጽሐፍ ቅዱስ
ከሚለው ጋር የሚጋጭ ከሆነ ሚዛናችንን መጣላችን እኮ ነው!
መፈተኛችንን ማስቀመጣችን እኮ ነው! መፈተኛው ከተጣለ ስሕተቱን
የማወቂያው መስፈርት ስለሚጠፋ ሁሉ ትክክል ነው ሊባል ነው። ግን
አይደለም። ይህ ምንጩን በተመለከተ ነው።
ውጤቱን በተመለከተ ደግሞ Agomoh የተጸለየላቸው ብዙዎች የኤች
አይ ቪ እና የካንሰር ሕሙማን እንደተፈወሱ ከተነገራቸው በኋላ ወደ
ቤታቸው ሄደው የሞቱ መሆናቸውን ተናግሮአል። አንዳንዶቹ ሰዎች
ከዊልቸር እንዲነሡና እንዲራመዱ የሚጠየቁት ቀድሞም ሽባዎች ያልሆኑ
ሰዎች ናቸው። Agomoh ከጠቀሳቸው ሰዎች አንዱ Maxwell Ijeh
የተባለው ሰው አእምሮው ታጥቦ (brain wash ተደርጎ) በዊልቸር
ተደርጎ የቀረበ ሰካራም እንጂ ሽባ አልነበረም። ዊልቸሩን ያቀረበውና
አእምሮውን አጥቦ ያስቀመጠው ራሱ Agomoh መሆኑን ተናግሮአል።
Wester Hoff የተባለው ሰው ደግሞ ቆሞ ረጅም ጊዜ መቆየትና
መራመድ አይችልም እንጂ መቆምም ጥቂት መንቀሳቀስም ይችላል።
ከመጣበት ዊልቸር ተነስቶ መቆሙና መራመዱ የማይችለው ሳይሆን
የሚችለው ነገር ነው፤ ዛሬም እንደዚያው በዊልቸር ነው ያለው። የጡትና
የአጥንት ካንሰር ተብለው የቀረቡት እነዚህ በጊዜ ውስጥ የሚደርቁ
ቁስሎች በመሆናቸው ቆይተው የደረቁ እንጂ ቀድሞም ካንሰር ያልነበሩ
ቁስልና የሚመግሉ እባጮች መሆናቸውንም ተናግሮአል። ስለዚህ እነዚህ
ፈውሶች ፈውሶች ያልሆኑ ቅጽበታዊ ፈውስ ያልተደረገላቸው ለትዕይንት
የቀረቡ እና ኋላ ሆስፒታል ሄደው በሕክምና ጭምር የዳኑ ናቸው።
እነዚህ በስፍራው በነበሩ የዓይን ምስክሮች ብቻ ሳይሆን ተባባሪ
አገልጋዮች በስም የተጠቀሱ ናሙና የሐሰት ፈውሶች ናቸው።
በምኩራቡ አገልጋዮች የኤድስ ፈውስ አዋጅ ታውጆላቸው
መድኃኒታቸውን እንዳይወስዱ የተነገራቸው ብዙ በሽተኞች
መሞታቸውን የለንደን ሕክምና ባለ ሥልጣኖች ገልጠዋል። 15
Agomohም ይህንኑ ሲያረጋግጥ ከተጸለየላቸው በኋላ በቤታቸውና
በሆስፒታል የሚሞቱት በሺህ የሚቆጠሩ ናቸው ብሎአል።
Nii Ayiku Amartey የተባለ የቲ. ቢ. የጋና አጋሩ የነበረ አገልጋይ፥ “ቲ.
ቢ. ጆሹዋ በ20 ሰዎች አካባቢ በተቀናበሩ ተአምራት የጋናን ሰዎች አስቶ
ነበር የገባው። ዛሬ ያኔ ተፈወሱ የተባሉት የተአምራት ተቀባዮች
20ዎቹም ሰዎች በሕይወት የሉም” ማለቱ ቀደም ሲል ተጠቅሶአል።
በወንጌል ውስጥ ጌታ ያደረጋቸው ፈውሶችና ከጌታ በኋላ በሐዋርያቱ እጅ
የተደረጉት ፈውሶች ብልጭ ብለው እልም ያሉ ፈውሶች ነበሩ ወይስ
የኖሩ?
በተቀባ ውኃ መፈወስስ? በዘመናችን ውኃ በብልቃጥ ሞልተው እየላኩ
መኖሪያ ያደረጉ ቸርቻሪዎች በዝተዋል። በምኩራቡም የተቀባ ውኃ
(Anointed Water) እየተባለ በ$50.00 ይሸጣል። ይህ በአገራችን
ጠበል ከሚባለው ምን ይለያል? በአገራችንማ ቧምቧ ፈንድቶ ፈንድቶ
ውኃ ሲወጣም ጠበል ነው እየተባለ ምስኪኑ ሕዝብ የተታለለባቸው
ጊዜዎች ስንት እንደሆኑ ማን ቆጠረው። ይህኛው ግን የተቀባ ውኃ
ሳይሆን የተቀመመ ውኃም መሆኑን Agomoh ገልጦታል። ከገበያም
ከሆስፒታልም የተገበዩ መድኃኒቶች የገቡበት ውኃ ፍሪጅ ውስጥ
እየተቀመጠ እዚያ የሚቆዩትና የሚጸለይላቸው በሽተኞች እንዲጠጡት
ይደረጋሉ ብሏል። ምናለበት መድኃኒቱ በድብቅ ሳይሆን በግልጽ እየተለካ
ቢሰጣቸው? ይህ ውኃ የሚጠጡት ብቻ ሳይሆን ይዘውት አጋንንታዊ
ተጽዕኖና መከራን የሚከላከሉበትም ነው። በቅርብ ያነበብኩት
በናይጄሪያ ይህንን ውኃ የያዘች አንዲት ሴት ከተገለበጠ አውቶቢስ
ውስጥ ሳትጎዳ እንደተረፈች ነው። የተጎዱት ብዙዎች ቢሆኑም
የተረፈችው እርሷ ብቻ አልነበረችምና ሌላው የተረፈው በከዘራዬ ወይም
በጫማ ማሰሪያዬ ነው ቢል ልዩነቱ ምን ሊሆን ነው?
ከሕመም የመዳን ፈውሶች በቅጽበትም ሆነ በሂደት የተፈጸሙባቸው
ታሪኮች በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በመጻፋቸውና ሕመም በጸሎትም፥
በመድኃኒትም፥ በጊዜ ውስጥ በመሻልም፥ በፍጥነትና አንዳንዴ በቅጽበት
በመጥፋትም ሊወገድ በመቻሉ ፈውስን ከተአምራት ጋር መቀየጥ
አይቻልም። በጸጋ ስጦታዎች ዝርዝር ውስጥም ከተአምራት ተለይቶ
መጻፉ ልዩነቱን ይገልጣል። የፈውስ ስጦታ በተግባር ሲገለጥ ግን እንደገና
ወደ ሆስፒታል ተወስዶ መሞት ወይም እንደነበሩ ሆኖ መቀጠል የለም።
ቁስልና መግልም እንኳ ቢሆን ፈውሱም ቅጽበታዊና ተአምራዊ ነው።
የውስጥ ሰዎቹ ምስክርነት የፈውሶቹን ሐሰትነት መግለጡ ፈውሶቹን
እጥያቄ ቀለበት ውስጥ ያስቀምጣቸዋል።
6) የተአምራት ምንነት ጥያቄ፤
ሰውን መቼም በቴሌቪዥን ማወቅና ከዚያ ባለፈ መመርመር የተለያዩ
ናቸው። ምልክቶችና ተአምራት የሚባሉ ነገሮች በተለይ በቴሌቪዥን
ለመሰራጨት ሲሰናዱ ዓላማቸውን ይስታሉ፤ ሰዎችንም ያስታሉ።
15 http://saharareporters.com/news-page/millionairenigerian-
pastor-tb-joshuas-church-linked-fraudulent-aidsclaims
19
ቁጥር 􀅧􀆅 - ግንቦት ፪ሺህ ፭ ezralit@gmail.com ዓመተ ምሕረት MAY 2013
በቴሌቪዥን የሚታዩ ተአምራት፥ ያውም ቀናት የፈጀ ጊዜ ወስደው
ተቀነባብረውና በአየር ላይ የሚለቀቁ ተአምራት በቀላሉ ሰዎችን
ሊያታልሉ ይችላሉ። የቢሶላ ምስክርነት ግልጽ ያደረገው እነዚህ
‘ተአምራት’ በጥንቃቄ የተሠሩና ተቀናብረው የተጣበቁ መሆናቸውን
ነው።
ተአምር በመጽሐፍ ቅዱስ እይታና አተረጓጎም በእግዚአብሔር ኃይል
አማካይነትና ለራሱ ለእግዚአብሔር ስም ክብር እንዲሁም ለልጆቹ
ጥበቃና ቤዛ የተፈጥሮ ሕግጋት ሲጣሱ ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ
ከታዩት መካከል የሞተ መነሣት፥ የባሕር መከፈል፥ የመና መውረድ፥
የፀሐይና ጨረቃ መቆም፥ የውኃ ወደ ወይም መለወጥ፥ የዕውር ማየት፥
የሽባ መነሣት፥ ወዘተ፥ ናቸው። እነዚህ ምልክትም ኃይልም ናቸው።
ያደረጋቸው የእግዚአብሔር ኃይል ሲሆን ምልክትነታቸው የሠሪውን፥
የአድራጊውን ማንነት መግለጥ ነው።
በቲ. ቢ. አገልግሎት ውስጥ ይህን የመሰለ ተአምር መፈጸሙ
አይታወቅም። የሞተ ሰው እንደተነሣ በአንድ ስርጭት ተላልፎአል። ነገር
ግን ይህም የተቀነባበረ የካሜራ ቴያትር መሆኑን በቦታው የነበሩቱ፥
ያቀነባበሩቱ፥ ከውስጡ የወጡቱ አጋልጠዋል። ቲ. ቢ. ስለ ፈውስ
ስጦታው እንደሚለው ከእናቱ ማኅጸን ሲወጣ እንዳገኘው የተፈጥሮ
ስጦታ ከሆነ ክርስቲያን ያልሆነም ሰው ፈውስም ሆነ ተአምርና ምልክት
ቢያደርግ፥ ሰዎች ተአምሩን ከጌታ የተደረገ ነው እንዳይሉ ምን
ያግዳቸዋል? እዚህ ላይ ነው ስሕተቱ! ተአምራት ብቻቸውን የአገልጋይ
ማንነት ምልክቶች አይደሉም። ተአምራት በሰዎች ኃይልና ጥበብ
የሚደረጉ ነገሮች አይደሉም። ይህ ማለት እግዚአብሔር ተአምራቱን
የሚሠራባቸው ሰዎች እርሱን የሚመስሉ መሆን አይጠበቅባቸውም
ማለት አይደለም።
ተአምራትን ግን ሰይጣንም ሊያደርግና ሊያስደርግ ስለሚችል
በምልክቶች በቀላሉ መወናበድ የለብንም። የፈርዖን አስማተኞች ምልክት
አድርገዋል። ከልብ እግዚአብሔርን ስለማይከተሉ ተአምረኞች ሲናገር
ዘዳ. 13፥1 ምልክትም ተአምራትም ቢሰጥህ ይላል። ምልክቶችና
ተአምራት የእግዚአብሔር ሰውነት አመልካቾች ላይሆኑ ይችላሉ።
በመጨረሻው ዘመን ሰይጣን በምልክትና ድንቆች ብዙዎችን
እንደሚያስት በሰፊው ተጽፎአል። ተአምራትን በተመለከተ
አመለካከታችን መጽሐፍ ቅዱስ ከሚለው ጋር የሚጋጭ ከሆነ ሚዛናችን
ይወድቅብናል። ሚዛናችን ከተጣለ ደግሞ መስፈርቱ ስለሚጠፋ ሁሉ
ትክክል ሳይሆን ትክክል ነው ሊባል ነው።
ደግሞም ከላይ ባየነው የተአምር ትርጉም መሠረት በዚህ ሰው
አገልግሎት የታዩ ተአምራት አለመኖራቸውንም እየተጤነ በኢየሱስ ስም
የተሠራ ተአምር ሁሉ በኢየሱስ የተሠራ ነው ብለን የምንቀበል ከሆንን
ለከፋ ስሕተት ራሳችንን መዳረጋችን መሆኑም መረሳት የሌለበት እውነት
ነው። ምክንያቱም በግልጥ የተነገረ ማስጠንቀቂያ አለን። በዚያ ቀን
ብዙዎች፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ በስምህ ትንቢት አልተናገርንምን፥
በስምህስ አጋንንትን አላወጣንምን፥ በስምህስ ብዙ ተአምራትን
አላደረግንምን? ይሉኛል። የዚያን ጊዜም፥ ከቶ አላወቅኋችሁም፤ እናንተ
ዓመፀኞች፥ ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ። ማቴ. 7፥22-23። ይህ
ክፍል በግልጥ የሚያስረዳን በስሙ ተአምራትን ያደረጉ ግን በእርሱ
ያልታወቁ ሰዎች መኖራቸውን ነው። ስለዚህ ተአምራት ዋናው
መታወቂያ አይደለም።
7) እንግዳ ጥንቆላዊ አሠራሮች ጥያቄ
እንግዳና በቤተ ክርስቲያን ሳይሆን በጠንቋዮች ቤቶች የሚታዩ እንግዳ
አደራረጎች በዚህ ሰው አገልግሎት ይታያሉ። አንዱ Mesmerism
የሚባለው ነው። ይህንን አንዳንድ ዘመናዊ ሳይኪያትሪስቶች
የሚጠቀሙበትም ሲሆን በቲ. ቢ. አገልግሎት እጅግ የሚታይ ነው። ይህ
የሰውየው እጅና ሰውነት እንቅስቃሴ የሌላውን ሰው ሰውነት
የሚቆጣጠርበት አሠራር ነው። አንዳንዶች Remote Control
Technique ይሉታል።
ይህ በቲ. ቢ. እና በሚያናግራቸው ወይም በሚደግምባቸው በሽተኞች
ሰዎች መካከል የማይታይ ገመድ ኖሮ እርሱ ያንን የማይታይ ገመድ
ሲስብ ሰዎቹ በጉባ ለመተኮስ ወይም ለመታረድ እንደሚጠለፍ በሬ
ተፈንግሎ መውደቅ፥ እጁን ሲያዞር በሽተኞቹ እሽክርክሪት ውስጥ
እንደገባ ሰው መሾርና ከመሽከርከራቸው የተነሣ ራሳቸውን ስተው
መውደቅ፥ እጁን ሲያወናጭፍ ተፈናጥረው መገንደስ፥ አየሩን ጠምዝዞ
ሲጥለው በትግል ሜዳ ውስጥ ያለ ታጋይ የሚታገለውን ሰው
እንደሚዘርረው መዘረር፥ እጁን ወደ ግራ ሲያዞር በሽተኛው ነፋስ
እንደገፋው ሰንበሌጥ ወደ ግራ፥ ወደ ቀኝ ሲያዞር ወደ ቀኝ መታጠፍ፥
እና ይህን የመሰሉ ትእይንቶችን ማየት የእያንዳንዱ ስርጭት ክፍል ነው
ማለት ይቻላል።
ይህን የመሰሉ ጨዋነት የጎደላቸው ብቻ ሳይሆን ጨዋነት ከቶም
የሌለባቸው ልምምዶች በአጠቃላይ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አይገኙም።
ኢየሱስ ሲፈውስ ሰዎችን ጠልፎ እየጣለ አልነበረም። ጳውሎስ ሰዎችን
እያንደባለለ አልፈወሰም። ጴጥሮስ ወይም ዮሐንስ ሰዎችን ጠምዝዘው
እየዘረሩ አልፈወሱም።
ሴቶች የግብረ ሥጋ አካላቸው ላይ አንዳች እንዳረፈበት እየተጋፉ
ሲከላከሉ፥ በመድረኩ ላይ ሽንታቸውን ሲስቱ፥ እዚያ ሽንት ላይ ሌሎች
ሲንደባለሉ፥ ሴቶች በሰልፍ እየተንፏቀቁ ከአንድ በኩል ወደ ሌላ
ሲሄዱ፥ እና እነዚህን የመሰሉ በብዙ የሚቆጠሩ ትእይንቶች ማየት
ከጨዋነት የራቀ አገልግሎት መሆኑን የሚመሰክሩ ናቸው።
Franz Anton Mesmer (1734-1815) የተባለ ኦስትሪያዊ ሐኪም ይህንን
አሠራር እንስሳዊ መግነጢስ ብሎ ሲሰይመው እንደ እርሱ እምነት ይህ
የሰውነት ነርቮች መግነጢሳዊ (magnetic) ኃይል በእጁ አድርጎ ሲወጣ
የበሽተኞችን እንቅስቃሴ መቆጣጠር ይችላል። ይህንን ነው Mesmerism
ብለው ሌሎች በስሙ የሰየሙት። በMesmer የተጠቀሱት ሌሎችም
ነገሮች ዓይን ሳይነቅሉ ትክ ብሎ በመመልከት የበሽተኛውን እንቅስቃሴ
ብቻ ሳይሆን አሳቡንም መቆጣጠር እንደሚችል ነው። Mesmer
የዘመናዊው hypnosis (ፍዘት) አባት ተብሎም ይጠራል። 16 እነዚህ
ነገሮች ቲ. ቢ. የሚያደርጋቸውም ናቸው። እነዚህ ከመጽሐፍ ቅዱስ
ውስጥ ያልተገኙ ከሆኑና በሌሎች ከጥንቆላ ባልተናነሱ ‘ሕክምና’ በተባሉ
ስፍራዎች የሚደረጉ ከሆኑ ምንጫቸው ከወዴት ነው? የሐዋርያት
አገልግሎት እኮ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ፈር የተቀደደበት ነው።
መከተል ያለብን በአዲስ ኪዳን የታየውን አገልግሎት መስመር ነው ወይስ
እንግዳ ጥንቆላዊ አሠራሮችን መስመር?
16 http://www.ltradio.org/articles/?admin=linkto&link=68
20
ቁጥር 􀅧􀆅 - ግንቦት ፪ሺህ ፭ ezralit@gmail.com ዓመተ ምሕረት MAY 2013
8) የትንቢት ዓላማ ጥያቄ / ትንቢት ምንድርነው?
በቲ. ቢ. ምኩራብ ውስጥ የተነገሩና የተፈጸሙ እየተባሉ የሚነገርላቸው
ትንቢቶች ቁጥር ብዙ ነው። አንዳንድ የፊልም ጠበብት የሆኑ ታዛቢዎች
እንዲያውም ትንቢቶቹ የተነገሩባቸውን ቁራጮች በማገናኘት ጥቂቶቹን
በማቅረብ ትንቢቶቹ ከተፈጸሙ በኋላ የተነገሩ መሆናቸውን ለማስረዳት
ሞክረዋል።
ደህና፤ ከመሆናቸው በፊት ተነገሩ ብንል እንኳ አንድ ነገር እንድንጠይቅና
መጽሐፍ ቅዱሳዊ መልስ እንድናገኝ ግድ ነው። የትንቢት ዓላማ
ምንድርነው? ከዚህ በፊት ትንቢት ራሱ ምንድር ነው?
ትንቢት ወደፊት የሚሆኑ ነገሮችን ብቻ መናገር ይመስለናል። አይደለም።
አለመሆኑን የትንቢት መጽሐፎች በግልጽ ያሳዩናል። በጣም ጥቂት ነገር
ወደፊት የሚሆነው የተጻፈባቸው አሉ። ስለ ወደፊቱ ጨርሶውኑ
ያልተነገረባቸውም የትንቢት መጽሐፎች አሉ። ስለዚህ ትንቢት
ስለሚሆነውና ስለሚመጣው መናገር ዋናው ነገሩ ሳይሆን ካለፈው
ተነሥቶ ስላለው ሁኔታ መናገር ነው።
ዓላማውስ? ዓላማው ደግሞ ማኅበርን ማነጽ ነው (1ቆሮ. 14፤ ኤፌ. 5)።
ማኅበር ማለት ደግሞ የክርስቶስ አካል ነው። አካል ሲባል ሰፊ ቢሆንም
በመጀመሪያ ደረጃ የሚታነጸው አጥቢያው ማኅበር ነው። የቲ. ቢ.
ትንቢቶች ለቤተ ክርስቲያንና ለቅዱሳን የሚጠቅሙና የሚያንጹ ናቸውን?
ለምሳሌ የአርሴናል ወይም የዛምቢያ እግር ኳስ ቡድን ማሸነፍ በትንቢት
መነገሩ ማንን ያንጻል? የእገሌ በፕሬዚደንትነት መመረጥ ወይም የዚህ
አገር የፕሬዚደንትነት የምርጫ ተወዳዳሪ መሞት የናይጄሪያን ወይስ
የጋናንና የማላዊን ቤተ ክርስቲያን ያንጻል? ኢንዶኔዥያ ውስጥ ወይም
አውስትሬሊያ አጠገብ የአውሮፕላን መከስከስ በኢንዶኔዥያ ያሉ እጅግ
ጥቂት ስደተኛ ክርስቲያኖችን እንዴት ያንጻል? ወይም ለአውስትሬሊያ፥
ቤተ ክርስቲያን የሚፈይደው ምንድርነው? ከትንቢቱ የተነሣ በዚምባብዌ
የደረሰበት አንድ ችግር ሰውየውን Morgan Tsvangirai እንደማይመረጥ
በመናገሩ የማላዊው መሪ Bingu wa Mutharika እንደሚሞት
የተናገረው ትንቢት ሳይሆን አስገድሎት ሳይሆን አይቀርም የሚል ክስም
ጭምር ነበር።
የማይክል ጃክሰንን ሞት ትንቢት በተመለከተ ከሞተ በኋላ ስለ እርሱ
የተነገረ መሆኑንና የትንቢቱንም መፈጸም ለማብሰር ተቀነባብሮ የቀረበ
አንድ ስርጭት ነበረበት። የዚህን ‘ትንቢት’ ግምታዊነት የሚገልጠው
ጠቅላላነቱ ነው። ‘በዚህ ዓመት አንድ ታዋቂ ሰው ይሞታል’ ተብሎ
የተጀመረው ትንቢት ማን መሆኑን አልተናገረም። ኋላ በናይጄሪያ ለነበረ
አንድ ሙዚቀኛ ማይክል በዚያ ዓመት እንደሚሞት ሳይሆን ወደ
ናይጄሪያ እንዲመጣና እንዲጸልይለት እንዲነግረው በጉባኤ ሳይሆን በግል
አሳሰበው። ቲ. ቢ. በየትም ሆኖ ሊጸልይለት ሲችል እንዲመጣ መፈለጉ
ለምን ይሆን? ኋላ ሲሞት ተንብዬ የነበረው ስለ እርሱ ነው አለ።
ሙዚቀኛውም ከቁም ነገር ስላልቆጠረው ይሆናል አልነገረውም፤ ማይክል
ሲሞት ግን አለመናገሩ ስሕተቱ መሆኑን እየተናዘዘ መሰከረ በምስክርነቱ
ቲ. ቢ. ነው ተጋንኖ የተደነቀው። ይህ ሁሉ እንደተጠበቀ ሆኖ ቲ. ቢ.
ማይክል ጃክሰን ወይም ሌላ ታዋቂ አቀንቃኝ ስም ጠርቶ በዚህ ዓመት
ወይም ቢዚያኛው ይሞታል ብሎ ቢተነብይ፥ ደግሞም ለዘላለም የሚኖር
ሰው አይደለምና በዚህ ዓመት ወይም በዚያ መሞቱ አይቀርምና ያ ሰው
ቢሞት የዚህ ትንቢት ለእግዚአብሔር ሕዝብ ጥቅሙ ከቶ ምንድርነው?
ማጠቃለያ ቃል
ከላይ በጥቂት አንቀጾች የተጠቀሱት ስምንት ነጥቦች እንደ መለኪያና ቲ.
ቢ.ን ብቻ ሳይሆን የምናያቸውን እና የምንሰማቸውን ሰባኪዎችና
አስተማሪዎች እንድንፈትሽ የሚያሳስቡን ነጥቦች ናቸው። በተለይ በዚህ
በዘመን መጨረሻ የምንገኝ ሰዎች ለእምነትም፥ ለክህደትም፥ ዋጋ
ለመክፈልም፥ በዋጋ ለማገልገልም፥ ለአስመሳይነትም፥ በአስመሳዮች
ለመወሰድም፥ የተጋለጥን ነን። አገልጋዮቻችንን ማክበር ሳይቀነስብን
ትምህርታቸውንና አካሄዳቸውን ላለመመርመር ጆሮቻችን፥ ዓይኖቻችንና
አፋችን የተዘጉ ሊሆኑ አይገባም።
ከሆነ ችግርን ወደ
ሕይወታችን ብቻ
ሳይሆን ወደ ቤተ
ክርስቲያናችንና ወደ
አገራችንም የምንጋብዝ
እና መርተን የምናስገባ
የታሪክም የትውልድም
ተጠያቂ እንሆናለን።
ማንንም ሰው ከውጭ ከምናየው ባሻገር በመጽሐፍ ቅዱስ መመርመርን
ልማዳችን ማድረግ ተገቢ መሆኑንም ላሳስብ እወዳለሁ። በቃሉ
ለመመርመር ደግሞ ቃሉን ማወቅ ተገቢ ነው። ቃሉም በመጀመሪያ
ደረጃ ሌላውን ለመመርመር ሳይሆን ራሳችንን ለመመርመርና ለመመገብ
ነው ማጥናት ያለብን። ከዚህ ጎንና ከዚህ እኩል ደግሞ በጸሎት የተለወሰ
የመለየት ስጦታም ያሻል። የመለየት ስጦታ በነዚህ ሁለት አጃቢዎች፥
በቃሉ ሙላትና በጸሎት ትጋት ሲያዝ ከአደጋ መጠበቅና ከሰለባነት መዳን
ይኖራል። ይህ እንዲሆንልን ጌታ ይርዳን።
ለአዲስ ኪዳን አገልግሎቶች መሠረት የሆነው ቅዱስ ቃሉና የጌታና
የሐዋርያት የአገልግሎት ፈር ነው። ይህም፥ ያም፥ ከሠራ፥ ውጤቱ
ከሰመረ፥ ፈውስ ካስመዘገበ፥ ሥልጣንና ምድራዊ አዱኛና በረከት ካስገኘ
እንውሰደው ብለን የምንሰበስበው ሳይሆን በቃሉ ውስጥ ይህን የመሰለ
ነገር ተደርጎአል? በቃሉ ውስጥ የምናያቸው እነጴጥሮስ፥ እነዮሐንስና
እነጳውሎስ እንዲህ ያደርጉ ነበር? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው።
ምልክቶች፥ ተአምራት፥ ቸርነቶችና ትልልቅ አገልግሎቶች መልካም ሳሉ
የአገልግሎት ስኬትና እውነተኛነት ብቸኛ መለኪያ ምልክቶች ማድረግ
ስሕተት መሆኑንም እንድናይ እወድዳለሁ። እነዚህን ሁሉ ነገሮች ሰይጣን
አሳምሮ መሥራትና በቀላሉ የሚያምኑ ሰዎችን ማታለል ይቻለዋል።
ተአምራት ዋናው መታወቂያ አይደለም። ከላይ በጠቀስኩት ጥቅስ
ልደምድም፤
በዚያ ቀን ብዙዎች፥ ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥ በስምህ ትንቢት
አልተናገርንምን፥ በስምህስ አጋንንትን አላወጣንምን፥ በስምህስ ብዙ
ተአምራትን አላደረግንምን? ይሉኛል። የዚያን ጊዜም፥ ከቶ
አላወቅኋችሁም፤ እናንተ ዓመፀኞች፥ ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ።
ማቴ. 7፥22-23። ይህ ክፍል በግልጥ የሚያስረዳን በስሙ ተአምራትን
ያደረጉ ግን በእርሱ ያልታወቁ ሰዎች መኖራቸውን ነው። እግዚአብሔር
ዘመናችንን፥ አገልጋዮቻችንን ከሁሉም በላይ እርሱን ጌታችንን በማወቅ
ሙላት ይባርከን።